Monday, July 17, 2017

Universalism ሰዎች ሁሉ ከሞት በሁዋላም ቢሆን ይድናሉ የሚለው የሐሰት አስተምህሮ

መፅሐፍ ቅዱስ በደንብ ካጠናነው ሁሉም ሰዎች ይድናሉ ወደሚል ድምዳሜ አያደርሰንም:: ቃሉ የሚለውን አጠቃላይ ሐሳቡን ካልተረዳን: ወደስሕተት የምንገባ ይመስለኛል:: እስቲ ቃሉ የሚለውን እንይ

የሚድኑት...
1. የተመረጡት
**ማቴ 24:31 "መላእክቱንም ከታላቅ መለከት ድምፅ ጋር ይልካቸዋል፥ ከሰማያትም ዳርቻ እስከ ዳርቻው ከአራቱ ነፋሳት ለእርሱ የተመረጡትን ይሰበስባሉ።"
**2 ቲሞ 2:10, 19 "ስለዚህ እነርሱ ደግሞ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለውን መዳን ከዘላለም ክብር ጋር እንዲያገኙ ስለ ተመረጡት በነገር ሁሉ እጸናለሁ።...19 ሆኖም፦ ጌታ ለእርሱ የሆኑትን ያውቃል፥ ደግሞም፦ የጌታን ስም የሚጠራ ሁሉ ከዓመፅ ይራቅ የሚለው ማኅተም ያለበት የተደላደለ የእግዚአብሔር መሠረት ቆሞአል።"
**ቲቶ 1:1-2 "የእግዚአብሔር ባሪያና የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የሆነ ጳውሎስ፥ በእግዚአብሔር ለተመረጡት እምነት እንዲሆንላቸው በዘላለምም ሕይወት ተስፋ እንደ አምልኮት ያለውን እውነት እንዲያውቁ የተላከ፤ ስለዚህም ሕይወት የማይዋሽ እግዚአብሔር ከዘላለም ዘመናት በፊት ተስፋ ሰጠ፥"

2. የተዘጋጁ...
**የሐዋ ሥራ 13:48 "አሕዛብም ሰምተው ደስ አላቸው የእግዚአብሔርንም ቃል አከበሩ፥ ለዘላለም ሕይወትም የተዘጋጁ ሁሉ አመኑ፤

3. ሰምተው የዳኑ...
**ዮሐ 5:24 "እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ቃሌን የሚሰማ የላከኝንም የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፥ ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻገረ እንጂ ወደ ፍርድ አይመጣም።"
**ኤፌ 1:13 "
እናንተም ደግሞ የእውነትን ቃል፥ ይኸውም የመዳናችሁን ወንጌል፥ ሰምታችሁ ደግሞም በክርስቶስ አምናችሁ፥ በተስፋው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ፤"

4. ያመኑ...
**ዮሐ 1:11-13 "የእርሱ ወደ ሆነው መጣ፥ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም።
ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤ እነርሱም ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከደም ወይም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከወንድ ፈቃድ አልተወለዱም።"
**ዮሐ 3:16.18.36 "በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።..18በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል።.. 36በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም።"
**ዮሐ 11:25-26 "ኢየሱስም፦ ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል፤ ሕያው የሆነም የሚያምንብኝም ሁሉ ለዘላለም አይሞትም፤ ይህን ታምኚያለሽን? አላት።"

እንዲህ እንዲህ እያልን ከጠቀስኩት በተጨማሪ ብዙ ማስረጃዎች ሰዎች በሕይወት እያሉ በክርስቶስ ካመኑ እንደሚድኑ ማስረጃዎችን መጥቀስ ሲቻል በተቃራኒው ደግሞ እንደቃሉ ያልኖሩ የሚደርስባቸውን ጥፋትና ፍርድ መጥቀስ እንችላለን

የሚጠፉት...
**ማቴ 7:21 "በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ፥ ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም።"

**ማር 10:45 "እንዲሁ የሰው ልጅም ሊያገለግልና ነፍሱን ለብዙዎች ቤዛ ሊሰጥ እንጂ እንዲያገለግሉት አልመጣም።"
#ብዙዎች ማለት ሁሉም ማለት አይደለም!

**ማር 3:28-29 "
እውነት እላችኋለሁ፥ ለሰው ልጆች ኃጢአት ሁሉ የሚሳደቡትም ስድብ ሁሉ ይሰረይላቸዋል፤
በመንፈስ ቅዱስ ላይ የሚሳደብ ሁሉ ግን የዘላለም ኃጢአት ዕዳ ይሆንበታል እንጂ ለዘላለም አይሰረይለትም።

**ዳን 12:2 "በምድርም ትቢያ ውስጥ ካንቀላፉቱ ብዙዎች ይነቃሉ፤ እኵሌቶቹ ወደ ዘላለም ሕይወት፥ እኵሌቶቹም ወደ እፍረትና ወደ ዘላለም ጕስቍልና።"

**ማቴ 18:9 "ዓይንህ ብታሰናክልህ አውጥተህ ከአንተ ጣላት፤ ሁለት ዓይን ኖሮህ ወደ ገሃነመ እሳት ከምትጣል ይልቅ አንዲት ዓይን ኖራህ ወደ ሕይወት መግባት ይሻልሃል።"

**ዮሐ 5:28-29 "
በመቃብር ያሉቱ ሁሉ ድምፁን የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል፤ መልካምም ያደረጉ ለሕይወት ትንሣኤ ክፉም ያደረጉ ለፍርድ ትንሣኤ ይወጣሉና በዚህ አታድንቁ።"

**ይሁዳ 7 "እንዲሁም እንደ እነርሱ ዝሙትን ያደረጉና ሌላን ሥጋ የተከተሉ ሰዶምና ገሞራ በዙሪያቸውም የነበሩ ከተማዎች በዘላለም እሳት እየተቀጡ ምሳሌ ሆነዋል።"

**2 ተሰ 1:8-10 "እግዚአብሔርን የማያውቁትን፥ ለጌታችንም ለኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል የማይታዘዙትን ይበቀላል፤ በዚያም ቀን በቅዱሳኑ ሊከብር፥ ምስክርነታችንንም አምናችኋልና በሚያምኑት ሁሉ ዘንድ ሊገረም ሲመጣ፥ ከጌታ ፊት ከኃይሉም ክብር ርቀው በዘላለም ጥፋት ይቀጣሉ።"

**ማቴ 25:41 "በዚያን ጊዜ በግራው ያሉትን ደግሞ ይላቸዋል፦ እናንተ ርጉማን፥ ለሰይጣንና ለመላእክቱ ወደ ተዘጋጀ ወደ ዘላለም እሳት ከእኔ ሂዱ።"


**ማር 14:21 "የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሄዳል፤ ነገር ግን የሰው ልጅ አልፎ ለሚሰጥበት ለዚያ ሰው ወዮለት፤ ያ ሰው ባልተወለደ ይሻለው ነበር አላቸው።"

ከብዙ በጥቂቱ ያላመኑ ሰዎች የሚደርስባቸውን የዘላለም ጥፋት ካየን በሁዋላ ይህን ጥቅስ ማየት ነገሮችን ሊያጠቃልልልን ይችላል

**ዕብ 9:27 "ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱ በኋላም ፍርድ እንደ ተመደበባቸው፥"

እንግዲህ ከላይ ያልኩትን ካልኩኝ በሁዋላ የዩንቨርሳሊዝም እምነት ተከታዮች ሁሉም ሰው ይድናል ብለው በሰፊው የሚጠቅሱትን ጥቅሶች እንይ

1. 1 ጢሞ. 2:3-4 "ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኃኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው።"

2. 2 ጴጥ. 3:9 "ለአንዳንዶች የሚዘገይ እንደሚመስላቸው ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም፥ ነገር ግን ሁሉ ወደ ንስሐ እንዲደርሱ እንጂ ማንም እንዳይጠፋ ወዶ ስለ እናንተ ይታገሣል።"

ስለነዚህ ጥቅሶች የተረዳሁትን ከማካፈሌ በፊት ይህን ጥቅስ እንይ ማቴ. 25:46 "እነዚያም ወደ ዘላለም ቅጣት፥ ጻድቃን ግን ወደ ዘላለም ሕይወት ይሄዳሉ።" እዚህ ጥቅስ ላይ ሁለት በግሪኩም አንድ የሆኑ "ዘላለም" በግሪኩ "aionion" የሆነ ቃል አለ በግልፅ እንደተቀመጠው አምነው የፀደቁ የዘላለም ሕይወት እንዳገኙ ሲናገር በተቃራኒው ደግሞ ያላመኑ የዘላለም ቅጣት እንደሚደርስባቸው ይናገራል

እዚህ ጋር የዩንቨርሳሊዝም ተከታዮች ፃድቃን የዘላለም ሕይወት እንደሚያገኙ ሲያምኑ ሃጥያአንን በተመለከተ ዘላለም የሚለውን ለተወሰነ ጊዜ እንጂ ለማያልቅ ጊዜ አይደለም ይላሉ ምንም እንኳ በግሪኩም ቢሆን ዘላለም የሚለው ቃል ለሁለቱም አንድ አይነት ቢሆንም

እንዲሁም በተመሳሳይ በ2 ጢሞ 4:18 "ጌታም ከክፉ ነገር ሁሉ ያድነኛል ለሰማያዊውም መንግሥት ይጠብቀኛል፤ ለእርሱ ከዘላለም እስከ ዘላለም ክብር ይሁን፤ አሜን።" በሚለው ቃሉ ላይ "ከዘላለም እስከ ዘላለም" የሚለው የጊዜ ወሰን የሌለው መጨረሻ የሌለው ክብር ለእግዝአብሔር ይሁን ሐዋርያው ጳውሎስ እንዳለ ሲቀበሉ በተቃራኒው ደግሞ በገሪኩም ተመሳሳይ ቃላት እዚህ ቃል ላይ ... ራዕ. 20:10 "ያሳታቸውም ዲያብሎስ አውሬውና ሐሰተኛው ነቢይ ወዳሉበት ወደ እሳቱና ወደ ዲኑ ባሕር ተጣለ፥ ለዘላለምም እስከ ዘላለም ቀንና ሌሊት ይሣቀያሉ።" .... "ከዘላለም እስከ ዘላለም"ሲል የጊዜ ወሰን አለው መጨረሻ አለው ብለው የቃሉን ትርጉም ይለውጡታል ምንም እንኳ ሁለቱም ቦታ የግሪኩ ቃል ተመሳሳይ eis tous aionos ton aionon ቢሆንም

አሁን ከላይ ወደጠቀስኩት ጥቅሶች ስመለስ...1 ጢሞ. 2:3-4 ... ጥቅሱን ስንረዳ እግዝአብሔር ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደማወቅ እንዲደርሱ ይወዳል ነገር ግን እሱ ይህን ቢወድም ሰዎች ሁሉ ግን እሱ ወዳሰበላቸው አይደርሱም ለምሳሌ እግዝአብሔር ሰዎች ሃጥያአትን እንዲሰሩ አይፈልግም አይወድም ሰዎች ግን በራሳቸው ፈቃድ ሃጥያአትን ይሰራሉ ስለዚህ እግዝአብሔር ሰዎች ሁሉ እንዲድኑ ቢወድም በሰዎች ምርጫ የተነሳ ሰዎች ሁሉ አይድኑም በሕዝቂየል 33 11 እንዲህ ይላል ..."እኔ ሕያው ነኝና ኃጢአተኛው ከመንገዱ ተመልሶ በሕይወት ይኖር ዘንድ እንጂ ኃጢአተኛው ይሞት ዘንድ አልፈቅድም፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ የእስራኤል ቤት ሆይ፥ ተመለሱ፥ ከክፉ መንገዳችሁ ተመለሱ ስለ ምንስ ትሞታላችሁ? በላቸው።"

በሌላም ቦታም እግዝአብሔር እንዲህ ይላል...ዮሐ 3:36 "በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም።" ስለዚህ እግዝአብሔር ሰዎች ሁሉ እንዲድኑ ወደእውነትም እንዲደርሱ ይወዳል እንጂ ከሰዎች ምርጫ የተነሳ ሰዎች ሁሉ አይድኑም ከአጠቃላይ የእግዝአብሔር ቃልና ሃሳብ ስንረዳ!

ወደሁለተኛው ጥቅስ ወደ 2 ጴጥ. 3:9 ስንሄድ ደግሞ እንዲሁ እንደመጀመርያው ተመሳሳይ መልስ ነው ያለው .. ሰዎች ሁሉ እንዲድኑ ጊዜ በመስጠት እግዝአብሔር ይታገሳል ነገር ግን እሱ ያን ሁሉ ቢታገስም ከክፉ መንገዳቸው ያልተመለሱ ሰዎች ወደዘላለም ጥፋት ይሄዳሉ

ሌላው ብዙ ጊዜ ዩንቨርሳሊስቶች ወደሚጠቅሱት ጥቅስ ስንሄድ....1 ጢሞ. 4:10 "ይህን ለማግኘት እንደክማለንና፥ ስለዚህም እንሰደባለን፤ ይህም ሰውን ሁሉ ይልቁንም የሚያምኑትን በሚያድን በሕያው አምላክ ተስፋ ስለምናደርግ ነው።"... አሁንም ይህን ጥቅስ ስናይ ከእዚህ ጥቅስ ተመሳሳይ የሆነውን ዩሐ 3 16 ስናይ..."በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።"... የእግዝአብሔር ዓላማ ዓለሙን ሁሉ ወይም ሰውን ሁሉ ማዳን ነው የሚወደው የሚፈልገውም ይህንን ነው ነገር ግን አሁንም ቃሉ እንደሚለን..." ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ፥ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አልላከውምና።
በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል።"... ከቃሉ እንደምንረዳው እግዝአብሔር ሰዎችን ሁሉ ለማዳን ቢወድም ያላመኑት ግን የሚጠብቃቸው የዘላለም ፍርድ ነው

ለማጠቃለል ሰዎች ሁሉ ይድናሉ ከሞት በሁዋላም የሚለው የዩንቨርሳሊዝም አስተምሮ ለምን አደገኛ እንደሆነ ልናገር...

የእዚህ እምነት አስተምሮ ተከታዮች ብዙዎቹ በድነት (Salvation) ውስጥ ባይሆኑም ወይም እንደቃሉ ባይኖሩም ብዙም አይገዳቸውም ምክንያቱም ከሞት በሁዋላም ንሰሐ የሚገቡበት እድል እንዳላቸው የእዚህ እምነት አስተምህሮን ስለሚነግራቸው ስለዚህ እንደቃሉ ለመኖር አይጨንቃቸውም ቃሉም አለመታዘዝ ብዙም አያስጨንቃቸውም ለሚያደርጉት እያንዳንዱ ነገር ዋጋ እንደሚያስከፍላቸው እንዲሁም በጊዜው ተናዘው መመለስ እንዳለባቸው ብዙም አይጨነቁበትም ምክንያቱም ከሞት በሁዋላ ሁለተኛ ዕድል አላችሁ ብሎ ዩንቨርሳሊዝም ስለሚያስተምራቸው

ሰይጣን የለም ብለው ስለሚክዱም የሰይጣንን አሰራርን አይረዱትም በእሱም የሐሰት አስተምህሮ ምክንያት የኢየሱስን አምላክነት ይክዳሉ የመንፈስ ቅዱስ አምላክነት ይክዳሉ ከእዚህም የተነሳ የመንፈስ ቅዱስን አብርሆነት ያጣሉ ቃሉን በትክክል አይረዱትም

ቃሉ ስለድነት ሲናገር እንዲህ ይላል...
**2 ቆሮ. 6:2 "በተወደደ ሰዓት ሰማሁህ በመዳንም ቀን ረዳሁህ ይላልና፤ እነሆ፥ የተወደደው ሰዓት አሁን ነው፤ እነሆ፥ የመዳን ቀን አሁን ነው።"... የመዳን ቀን ዛሬ ነው ከሞት በሁዋላ አይደለም
**ዕብ. 4:7 "ዛሬ ድምፁን ብትሰሙት ልባችሁን እልከኛ አታድርጉ በፊት እንደ ተባለ፥ ይህን ከሚያህል ዘመን በኋላ በዳዊት ሲናገር፦ ዛሬ ብሎ አንድ ቀን እንደ ገና ይቀጥራል።“Today,” saying through David after so long a time just as has been said before, “Today if you hear His voice, Do not harden your hearts"

Tuesday, February 28, 2017

በብሉይ ኪዳን መጽሐፍት በብዙ ቦታዎች የተጠቀሰው የጌታ መልአክ ማነው???

ጳውሎስ ፈቃዱ እንደጻፈው

 “ያሕዌ” እና “የያሕዌ መልአክ”
ከእግዚአብሔር ወልድ የዘላለም ልጅነት ጋር የሚጣጣሙ ማስረጃዎች በብሉይ ኪዳንም አሉ። ለምሳሌ እግዚአብሔር በሚነድድ ቊጥቋጦ መካከል ለሙሴ የተገለጠበትን መንገድ ማጤን ይቻላል (ዘፀ. 3፥1 - 4፥17)። ታሪኩ ሲጀምር ለሙሴ የተገለጠው አካል፣ “የእግዚአብሔር መልአክ” ተብሎ ነው የተዋወቀው (3፥2)። ከዚያ በኋላ ግን፣ በታሪኩ ውስጥ “የእግዚአብሔር መልአክ” መባሉ ቀርቶ “እግዚአብሔር” እየተባለ ነው የቀረበው (3፥4፡6፡7፤ 4፥2፡4፡5፡6፡10፡11፡14)። ሙሴም የሚያነጋረውን አካል ስም ሲጠይቅ፣ “ያለና የሚኖር” ወይም “ያህዌ (יהוה)” የሚል ምላሽ አግኝቷል (3፥14)። ተናጋሪው አካል፣ “እኔ የአባትህ አምላክ፣ የአብርሃም አምላክ፣ የይስሐቅ አምላክ፣ የያዕቆብም አምላክ ነኝ” በማለት ራሱን ለሙሴ አስተዋውቋል (3፥6፡15)። በተጨማሪም በንግግሩ ውስጥ ሁሉ፣ “የሕዝቤን ጩኸት ሰማሁ፤ መከራቸውን አየሁ፤ አድናቸዋለሁ፤ ከግብፅ አወጣቸዋለሁ፤ አንተንም እልክሃለሁ፤ ወዘተ.” በማለት የአንደኛ መደብ ቋንቋን ነው የሚጠቀመው። እሳት ከእግዚአብሔር መገለጥ ጋር እንደሚያያዝም ይታወቃል (ዘፀ. 13፥21-22፤ 19፥18፤ 40፥38፤ 1ነገ. 18፥24፡38)። ታዲያ ይህ መልአክ ማነው?   

ለያዕቆብ የተገለጠለትም “መልአክ” ራሱን “የቤቴል አምላክ እኔ ነኝ” በሚል ነው የገለጠው (ዘፍ. 31፥11-13)። በሌላ ስፍራ ደግሞ፣ ኀጢአትን  ይቅር የማለትና ያለ ማለት ሥልጣን ያለው ሆኖ ቀርቧል (ዘፀ. 23፥20-21)። እስራኤላውያንን ከግብፅ ያወጣው እርሱ መሆኑን፣ ከእነርሱም ጋር የገባውን ቃል ኪዳን እንደሚጠብቅ፣ እነርሱ ግን የገቡለትን ቃል ባለመጠበቃቸው ማዘኑንም ይናገራል (መሳ. 2፥1-3)። ለጌዴዎን ሲገለጥም (መሳ. 6፥11-24)፣ “የእግዚአብሔር መልአክ” (ቊ. 11፡12፡20፡21) እና “እግዚአብሔር” (ቊ. 14፡16፡20) እየተባለ ተጠርቷል። በዘካርያስ 12፥8ም በዚሁ መልክ ተጠቅሷል። በአዲስ ኪዳን ውስጥ በዚህ መልኩ ከእግዚአብሔር ጋር አንድ ሆኖ የተገለጠ መልአክ የለም።[36] ለምን?

ለእነዚህ ጥያቄዎች ምላሽ ለማግኘት፣ “መልአክ” ከሚለው ቃል ትርጓሜ መጀመር ግድ ይሆናል። መልአክ በዕብራይስጥ ማላክמַלְאָך) ) ሲሆን፣ መልአክ፣ መልእክተኛ፣ ልዑክ የሚሉ ትርጓሜዎችን ይዟል።[37] (የሚገርመው ነገር በግሪኩም ትርጓሜው ይኸው መሆኑ ነው![38]) ለምሳሌ፣ በምሳሌ 17፥11 የሚገኘውን ይህንኑ “ማላክ” የተሰኘ ቃል፣ የ1954 የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ “መልአክ” ሲለው፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም እና የ1997 ትርጕም “መልእከተኛ” ብለውታል። በ2ኛ ነገሥት 1፥3 ውስጥ 2 ጊዜ የሚገኘው ይኸው ቃል፣ በዚያው ጥቅስ ውስጥ “መልአክ” እና “መልእክተኞች” ተብሎ ነው የተተረጐመው። በዕብራይስጡ “ማላከ ሞት” (מַלְאָךְ מָוֶת) የሚለው ስያሜ “የሞት መልእክተኛ” (ምሳሌ 16፥14)፣ “ማልአክ ሻሎውም” (מַלְאָךְ שָׁלֹום) ደግሞ “የሰላም መልእክተኞች” (ኢሳ. 33፥7) ተብሏል።[39] ማላክ የሚለው ቃል በብሉይ ኪዳን ውስጥ 213 ጊዜ ሲገኝ፣ ለምሳሌ NIV መጽሐፍ ቅዱስ፣ 108 ጊዜ መልአክ/መላእክት፣ 83 ጊዜ መልእክተኛ/መልእክተኞች፣ 8 ጊዜ ደግሞ ልዑክ/ልዑካን (envoy, delegation, official) በማለት ተርጕሞታል።[40]

ስለዚህ ይህ “የቤቴል አምላክ”፣ “የአብርሃም፣ የይስሐቅ፣ የያዕቆብ አምላክ” የሆነውና “ያሕዌ ነኝ” ያለው “መልአክ” በእርግጥም ያህዌ መሆኑ እንደማያጠራጥር ሁሉ፣ መልእክተኛ (የተላከ) መሆኑም አያጠራጥርም። ይህ ደግሞ አስቀድመን ካነሣነው ሐሳብ ጋር ይገጥማል። እግዚአብሔር ወልድ፣ የእግዚአብሔር አብ ልጅ የሆነው ከዘላለምም ነውና በብሉይ ኪዳን የአባቱ መልእከተኛ በመሆን (እየተላከ) ይመጣ እንደ ነበር መናገር ይቻላል። እርሱ ያሕዌም፣ የያሕዌ መልእክተኛም ነው። አብ በአባትነቱ ወልድን ይልካል፤ ወልድም በልጅነቱ ለአብ ይላካል! የእግዚአብሔር መልአክ የተሰኘው፣ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ከመምጣቱ በፊት (ቅድመ ትስጉት) የተገለጠበት መገለጫ ማንነቱ ነበር። ከሙሴ በፊት፣ ለአብርሃምም፣ ለአጋርም፣ ለያዕቆብም የተገለጠው ያ እግዚአብሔር ወልድ ነው።

Friday, April 8, 2016

የPaul C Jong የውሃና መንፈሱ የተለየ ወንጌል

ዌብሳይት ላይ ወይም በሰዎች ወይም መንገድ ላይ በነፃ ወይም በትንሽ ብር Paul C Jong የውሃና መንፈሱ ወንጌል የሚል መፅሐፍ አግኝተው አንብበው ይሆን ከሆነ እነዚህ አስተውሉ...

1. ለመዳን ኢየሱስ በመጥምቁ ዮሐንስ ሲጠመቅ የዓለም ሁሉ ሃጥያአት እንደተላለፈበት ከመስቀሉ ሞት በተጨማሪ ማመን አለቦት ይሎታል መፅሐፉ

2. አንዴ በእነሱ ወንጌል አምነው ከዳኑ በሁዋላ እርሶ ሃጥያአት ቢሰሩ ችግር የለውም ሃጥያአቶ ይቅር ስለለተባሉ ይሎታል መፅሐፉ

3. በክርስትና ሕይወቶ ምንም ሃጥያአት ቢሠሩ መናዘዝ አያስፈልግም ይሎታል

ይህ ቃሉ ከሚያስተምረን የተለየ ወንጌል ስለሆነ ይጠንቀቁ!!!

የእግዝአብሔር ቃል ሲያስተምረን...

ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም ተወልዶ ከእሱ በፊት በተላከው መጥምቁ ዮሐንስ መጠመቁን ከእዛም ማገልገሉን በመጨረሻም ሃጥያአታችንን በመስቀል ላይ ተሸክሞ ደሙን በማፍሰስ ዋጋ እንደከፈለልን በሶስተኛው ቀን እንደተነሳ ከእዛም ከጥቂት ጊዜ በሁዋላ እንዳረገ አሁን ተመልሶ እስኪመጣ ድረስ በአባቱ ቀኝ እንዳለ እንደተፃፈው እንደቃሉ እናምናለን

ከእዚህ በተረፈ
1. መጥምቁ ዮሐንስ ሊቀ ካህን ነው የሚለውን Paul C Jong ፍልስፍና አናምንም:: ምክንያቱም መጥምቁ ዮሐንስ በነበረበት ጊዜ ሊቀ ካህን የነበረው ቀያፋ እንደነበር ነው ቃሉ የሚያስተምረው:: በአንድ ወቅት ደግሞ ሁለት ሊቀ ካህን በምድር ሊኖር አይችልም::

Paul C Jong መጥምቁ ዮሐንድ ሊቀ ካህን ነው የሚል መፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንደሌለ አልጠፋውም ነገር ግን በማጠጋጋት ኢየሱስ እንዲህ ያለውን " እነሆ፥ መንገድህን በፊትህ የሚጠርግ መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ ተብሎ የተጻፈለት ይህ ነውና። እውነት እላችኋለሁ፥ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም፤ በመንግሥተ ሰማያት ግን ከሁሉ የሚያንሰው ይበልጠዋል።"

ይህ ጥቅስ መጥምቁ ዮሐንስ ሊቀ ካህን እንደሆነ በፍፁም አይናገረም ቃሉን ምንም መተንተን ሳያስፈልገን መጥምቁ ዮሐንስ ማን እንደሆነ ኢየሱስ ራሱ ይነግረናል እንዲህ ብሎ... "እነሆ፥ መንገድህን በፊትህ የሚጠርግ #መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ"... ስለዚህ ምንም እንኩዋ መጥምቁ ዮሐንስ የሌዊ የካህናት ወገን ቢሆንም መልዕከተኛ እንጂ ሊቀ ካህን አይደለም አልነበረምም

ምናልባት እንዲህ የሚለውን ብናይ..."ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም፤"... ይህ ሊቀ ካህን መሆኑን ሳይሆን የሚናገረው ከሌሎች ነቢያት ይልቅ ከእናቱ ማህፀን ጀምሮ በመንፈስ ቅዱስ የተሞላ መሆኑ ምሳሊያዊ የሆነ ሕይወቱ መልዕክቱ የተለየ መሆኑ የተላከበት መልዕክት ከሌሎቹ የተለየ መሆኑ የክርስቶስን መንገድ የሚጠርግ የሚያዘጋጅ መሆኑ ስለክርስቶስ በአካል እያሳየ የመሰከረ መሆኑ ከሌሎች ነቢያት ሁሉ ያስበልጠዋል ይህ ነው እንጂ የሚለየው በፍፁም ሊቀ ካህን አልነበረም የእግዝአብሔር ቃልም ሊቀ ካህን ነበረ አይለንም

በእነሱ እምነት ሰው ይድናል የሚሉት: ""ኢየሱስ ክርስቶስ መጥምቁ ዮሐንስ (በእነሱ ሊቀ ካህኑ) ኢየሱስን ሲያጠምቀው: የዓለምን ሁሉ ሃጥያአት በኢየሱስ ላይ ጫነበት ወይም አስተላለፈበት:: ይህንን ጨምሮ በመስቀል ላይ ዋጋ መክፈሉን ስናምን እንድናለን ነው::""" ነገር ግን Paul C Jong በእዚህ በመጥምቁ ዮሐንስ ላይ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ ከደህንነት ጋር አያይዞ የሚሰብከውን ነገር: መፅሐፍ ቅዱስ ግን በእዛ መልኩ በፍፁም አልጠቀሰውም:: እንዲያው ጳውሎስ የሚሰብከው ወንጌል ምን አይነት እንደሆነ ሲናገር እንዲህ ነው ያለው...

1ቆሮ 15:1-4 "ወንድሞች ሆይ፥ የሰበክሁላችሁን ደግሞም የተቀበላችሁትን በእርሱም ደግሞ የቆማችሁበትን በእርሱም ደግሞ የምትድኑበትን ወንጌል አሳስባችኋለሁ፤ በከንቱ ካላመናችሁ በቀር፥ ብታስቡት፥ በምን ቃል እንደ ሰበክሁላችሁ አሳስባችኋለሁ። እኔ ደግሞ የተቀበልሁትን ከሁሉ በፊት አሳልፌ ሰጠኋችሁ እንዲህ ብዬ። መጽሐፍ እንደሚል ክርስቶስ ስለ ኃጢአታችን ሞተ፥ ተቀበረም፥ መጽሐፍም እንደሚል በሦስተኛው ቀን ተነሣ" Paul C Jong እምነት: ዋና መሠረት የሆነውን: የመጥምቁ ዮሐንስ የዓለምን ሃጥያአት ሁሉ በኢየሱስ ላይ አስተላለፈ የሚለውን: በፍፁም አልጠቀሰውም:: ለምን ሐዋርያቶች በመልዕክታቸው: አንዴም እደግመዋለሁ: አንዴም ይህ አስተማሪያችሁ: ዋና ነው የሚለውን አልጠቀሱም??

ይልቅስ ለመዳን የሚያስፈልጉትን ቃሉ በግልፅ የሚነግረን እንዲህ ብሎ ነው...

የሐዋ ሥራ 16:30-31 "ወደ ውጭም አውጥቶ። ጌቶች ሆይ፥ እድን ዘንድ ምን ማድረግ ይገባኛል? ኣላቸው። እነርሱም። በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ እመን አንተና ቤተ ሰዎችህ ትድናላችሁ አሉት።"

ሮሜ 10:9-10 "ኢየሱስ ጌታ እንደ ሆነ በአፍህ ብትመሰክር እግዚአብሔርም ከሙታን እንዳስነሣው በልብህ ብታምን ትድናለህና፤ ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና በአፉም መስክሮ ይድናልና።"

ኤፌ 2:8 "ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፤

ከእዚህ ውጪ በዮሐንስ ጥምቀት ማለትም የዓለምን ሃጥያአት ሁሉ በኢየሱስ ላይ ጫነ የሚል ትምህርት መፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሳይሆን የሚገኘው Paul C Jong ፍልሰፍና መፅሐፍ በቻ ነው::

*** መፅሐፍ ቅዱስ ሲያስተምረን ድነት(Salvation) ወይም ፅድቅ(Justification) ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ በሠራልን ሥራ በእምነት የምናገኘው ነገር ነው

*** ቅድስና (Sanctification) እኛ ከዳንን በሁዋላ በቃሉና በመንፈስ ቅዱስ እያደግን የምናፈራው ፍሬ ነው

አንድ የዳነ ሰው በሕይወቱ ፍሬ ማፍራት አለበት:: እንደሚያፈራው ፍሬም ሽልማት አለው:: ፍሬ (መልካም ሥራ) ለማፍራት ራሱን ወይም መንፈሱን: በእግዝአብሔር ቃል: በፀሎት: ሕብረት በማድረግ: በመፆም: በመሳሰሉት... መንፈሱን በመመገብ ራሱን ማሳደግ አለበት:: መንፈሱን ሁሌ የሚመግብ ሰው በሕይወቱ የመንፈስ ፍሬ ይታይበታል::

ቃሉ እንደሚነግረን የመንፈስ ፍሬ እነዚህ ናቸው::
ገላ 5:22 "የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ትዕግሥት፥ ቸርነት፥ በጎነት፥ እምነት፥ የውሃት፥ ራስን መግዛት ነው።"

ስለዚህ በቃሉ የምንደገፍ እና የምንታመን ከሆነ ከአንድ የዳነ ሰው እነዚህ ፍሬዎች ይጠበቃሉ በአፉ ድኛለሁ እያለ በተግባር ወይም በሕይወቱ የሚታየው ሃጥያአት ከሆነ ራሱን ያታልላል እንጂ አልዳነም መጨረሻው ገሃነም ነው

ስለዚህ ቃሉ እንደሚል ሰው የሚድነው በእምነት ብቻ እንጂ በእምነትና በሥራ አይደለም:: ነገር ግን አንድ የዳነ ሰው በሕይወቱ ፍሬ መታየት አለበት የሚታየው ግን የሥጋ ሥራ ብቻ ከሆነ አልዳነም

ለመጨመር ያህል ቃሉ እንዲህ ይላል...
ያዕ 1:22 "ቃሉን የምታደርጉ ሁኑ እንጂ ራሳችሁን እያሳታችሁ የምትሰሙ ብቻ አትሁኑ።"

1 ጴጥ 1:14-15 "እንደሚታዘዙ ልጆች ባለማወቃችሁ አስቀድሞ የኖራችሁበትን ምኞት አትከተሉ። ዳሩ ግን። እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ ተብሎ ስለ ተጻፈ የጠራችሁ ቅዱስ እንደ ሆነ እናንተ ደግሞ በኑሮአችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ።"

ሮሜ 6:11-18 "እንዲሁም እናንተ ደግሞ ለኃጢአት እንደ ሞታችሁ፥ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ሆናችሁ ለእግዚአብሔር ሕያዋን እንደ ሆናችሁ ራሳችሁን ቈጠሩ። እንግዲህ ለምኞቱ እንድትታዘዙ በሚሞት ሥጋችሁ ኃጢአት አይንገሥ፤ ብልቶቻችሁንም የዓመፃ የጦር ዕቃ አድርጋችሁ ለኃጢአት አታቅርቡ፥ ነገር ግን ከሙታን ተለይታችሁ በሕይወት እንደምትኖሩ ራሳችሁን ለእግዚአብሔር አቅርቡ፥ ብልቶቻችሁንም የጽድቅ የጦር ዕቃ አድርጋችሁ ለእግዚአብሔር አቅርቡ። ኃጢአት አይገዛችሁምና፤ ከጸጋ በታች እንጂ ከሕግ በታች አይደላችሁምና። እንግዲህ ምን ይሁን? ከጸጋ በታች እንጂ ከሕግ በታች ስላይደለን ኃጢአትን እንሥራን? አይደለም። ለመታዘዝ ባሪያዎች እንድትሆኑ ራሳችሁን ለምታቀርቡለት፥ ለእርሱ ለምትታዘዙለት ባሪያዎች እንደ ሆናችሁ አታውቁምን? ወይም ለሞት የኃጢአት ባሪያዎች ወይም ለጽድቅ የመታዘዝ ባሪያዎች ናችሁ። ነገር ግን አስቀድማችሁ የኃጢአት ባሪያዎች ከሆናችሁ፥ ለተሰጣችሁለት ለትምህርት ዓይነት ከልባችሁ ስለ ታዘዛችሁ፥ ከኃጢአትም አርነት ወጥታችሁ ለጽድቅ ስለ ተገዛችሁ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን።"

*** እንግዲህ በግልፅ በእግዝአብሔር ቃል እንደምናየው አንዴ በኢየሱስ አምነን ከዳንን በሁዋላ ሰው ስለሆንን ሃጥያአት እየሠራን መቀጠል ትችላላችሁ በፍፁም በፍፁም አይልም:: ሃጥያአት የመስራት ፈቃድ (Licence) አልተሰጠንም::

ቃሉ የሚለው በተቃራኒው...
ቅዱሳን ሁኑ
የድሮውን ምኞታችሁን አትከተሉ
ቃሉን አድርጉ
የኃጢአት ባሪያዎች አትሁኑ
ኃጢአት አይገዛችሁም
ብልቶቻችሁንም የጽድቅ የጦር ዕቃ አድርጋችሁ ለእግዚአብሔር አቅርቡ
ብልቶቻችሁንም የዓመፃ የጦር ዕቃ አድርጋችሁ ለኃጢአት አታቅርቡ፥
በሥጋችሁ ኃጢአት አይንገሥ

ይህንን ነው የእግዝአብሔር ቃል አጥብቆ የሚነግረን::

ስለዚህ ወንድሞቼና እህቶቼ ሰው ስለሆንን ሃጥያአት ከመፅራት ልንቆጠብ አንችልምና ብንሠራ ችግር የለውን አንዴ በመስቀል ላይ ወይም በዮሐንስ ጥምቀት ተወግዶልናል የሚል ትምህርት መፅሐፍ ቅዱሳዊ አይደለም::

*** ሰው ከዳነ በሁዋላ ሃጥያአት አይሰራም??
እንደሰዉ ዓይነት የሚሠራው ሃጥያአት ሊበዛም ሊያንስም ይችላል እንጂ ሃጥያአት መሥራቱ አይቀርም

*** ታዲያ ሃጥያአት ቢሠራ ምን ያድርግ??
የእግዝአብሔር ቃል እንዲህ ይለናል
1 ዮሐ 2:1 " ልጆቼ ሆይ፥ ኃጢአትን እንዳታደርጉ ይህን እጽፍላችኋለሁ። ማንም ኃጢአትን ቢያደርግ ከአብ ዘንድ ጠበቃ አለን እርሱም ጻድቅ የሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።"
ያዕ 5:16 "እርስ በርሳችሁ በኃጢአታችሁ ተናዘዙ። ትፈወሱም ዘንድ እያንዳንዱ ስለ ሌላው ይጸልይ፤ የጻድቅ ሰው ጸሎት በሥራዋ እጅግ ኃይል ታደርጋለች።"

****ኑዛዜ Confession እና ንሰሃ Repentance የሚያመሳስላቸው ነገር እንዳለ ሁሉ የሚለያያቸውም ነገር አለ

አንድ ሰው መጀመርያ: የእግዝአብሔርን ቃል አንብቦ: ወይም ሰምቶ: ሃጥያአተኝነቱን አውቆ: ሃጥያአቱን ተናዞ (Confessed) ንሰሃ ከገባ (Repent) ኢየሱስ በመስቀል ላይ ደሙን አፍስሶ ዋጋ እንደከፈለለት አምኖ ከተቀበለ ሰው ሃጥያአቱ በሙሉ ተሰርዮለታል::

ንሰሃ (Repentance) ማለት: የኑሮውን: የአስተሳሰቡን ወይም በሥጋ መመላለሱን: ቀይሮ በመንፈስ መመላስ የሕይወቱን አቅጣጫ መቀየሩን የሚያሳይ ነው::

ስለዚህ እንዲህ ንሰሃ የገባ ሰው ድነትን ስላገኘ ከፍርድ አምልጥዋል::

ይህ የዳነ ክርስትያን በሕይወቱ ሲኖር: ሃጥያአት መሥራቱ አይቀርም:: ይህም ከአምላኩ ጋር ያለውን ግንኙነት ያበላሸዋል:: ስለዚህ ሃጥያአት መሥራቱን በተገነዘበ ቁጥር ለአምላኩ መናዘዝ (confess) አለበት::

የእግዝአብሔር ቃል የሚለውን እንይ...
1ዮሐ1:6-10 "ከእርሱ ጋር ኅብረት አለን ብንል በጨለማም ብንመላለስ እንዋሻለን እውነትንም አናደርግም፤ ነገር ግን እርሱ በብርሃን እንዳለ በብርሃን ብንመላለስ ለእያንዳንዳችን ኅብረት አለን፥ የልጁም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻናል። ኃጢአት የለብንም ብንል ራሳችንን እናስታለን፥ እውነትም በእኛ ውስጥ የለም። በኃጢአታችን ብንናዘዝ ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን ከዓመፃም ሁሉ ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው። ኃጢአትን አላደረግንም ብንል ሐሰተኛ እናደርገዋለን ቃሉም በእኛ ውስጥ የለም።"

ከእዚህ የእግዝአብሔር ቃል የምንረዳው መጀመርያ ይህን መልዕክት ሐዋርያው ዮሐንስ የፃፈው ህብረት አለን ለሚሉ በብርሃን ለሚመላለሱ ለዳኑ ክርስትያኖች ነው:: ለእነዚህ ክርስትያኖች...."ኃጢአት የለብንም ብንል ራሳችንን እናስታለን፥ እውነትም በእኛ ውስጥ የለም።"... ይላቸዋል:: ምክንያቱም ወደፍፁምና ገና ስላልደረሱ: በሕይወታቸው ሃጥያአትን መሥራታቸው አይቀርም:: ስለዚህ ሃጥያአታቸውን እንዲናዘዙ ይነግራቸዋል ይመክራቸዋል::

ከእዛም ይቀጥልና እንዲህ ይላል... 1ዮሐ 2:1 "ልጆቼ ሆይ፥ ኃጢአትን እንዳታደርጉ ይህን እጽፍላችኋለሁ። ማንም ኃጢአትን ቢያደርግ ከአብ ዘንድ ጠበቃ አለን እርሱም ጻድቅ የሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።"...

አንድ ፀጋውን አምኖ የዳነ ክርስትያን: መጀመርያ ንሰሃ የገባ ጊዜ: ሃጥያአቱ ሁሉ ተሰርዮለታል:: ይህ ማለት ግን በሰዋዊው ተፈጥሮ ምክንያት: በሕይወቱ በኑሮው ሃጥያአትን እንዲሰራ ፈቃድ አግኝትዋል ማለት አይደለም:: ቃሉም እንደሚል...
ሮሜ 6:15 "እንግዲህ ምን ይሁን? ከጸጋ በታች እንጂ ከሕግ በታች ስላይደለን ኃጢአትን እንሥራን? አይደለም።"

ስለዚህ የዳነ ሰው ገና ለገና ሃጥያአቱ ሁሉ ስለተሰረየለት: ሃጥያአትን የመሥራት ፈቃድ የለውም:: ግን አሁንም ቃሉ እንደሚል...."ኃጢአት የለብንም ብንል ራሳችንን እናስታለን፥ እውነትም በእኛ ውስጥ የለም።"...ሃጥያአትን መሥራቱ አይቀርም:: ለእዚህ ከድነት በሁዋላ ለሚሠራው ሃጥያአት መናዘዝ አለበት:: አሁን ቃሉ እንደሚለው.."በኃጢአታችን ብንናዘዝ ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን ከዓመፃም ሁሉ ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው።"

ሌላም ቦታ ሐዋርያው ያዕቆብ እንዲህ ይላል.... ያዕ 5 16 "እርስ በርሳችሁ በኃጢአታችሁ ተናዘዙ።"

ለማጠቃለል: ቃሉም ስለሚያዝ: አንድ የዳነ ክርስትያን ሃጥያአት የማድረግ ፈቃድ የለውም:: ሃጥያአትን ቢሰራ ግን በሰማይ ጠበቃ ስላለው ሃጥያአቱን መናዘዝ አለበት::
ነገር ግን አንዴ በንሰሃ ሃጥያአቴ ሁሉ ይቅር ስለተባለ: ደግሞም በተፈጥሮዬ ሰው ስለሆንኩኝ: ሃጥያአትም መሥራቴ ስለማይቀር: ኑዛዜ አያስፈልገኝም: ዝም ብዬ እንደተለመደው ሃጥያአት እየሰራሁ እቀጥላለሁ ሰው ስለሆንኩ የምንል ከሆነ: ቃሉ እንዲህ ይለናል....

ዕብ 10:26-27 "የእውነትን እውቀት ከተቀበልን በኋላ ወደን ኃጢአት ብናደርግ ከእንግዲህ ወዲህ ስለ ኃጢአት መሥዋዕት አይቀርልንምና፥ የሚያስፈራ ግን የፍርድ መጠበቅ ተቃዋሚዎችንም ሊበላ ያለው የእሳት ብርታት አለ።"